“አትፍራ… ዋጋህም እጅግ ታላቅ ነው”

በፀሐይ ዓለሙ

ጌታ እግዚአብሔር ለአብራም ይህን ቃል የተናገረው ከጦርነት እንደ ተመለሰ ነው። ጦርነቱ አልቆ ድል አድርጐ ከተመለሰ በኋላ አብራምን ምን የሚያስፈራ ነገር ገጠመው?

አብራም የእምነት ሰው መሆኑ ይነገርለታል፤ እምነትና ፍርሃት ደግሞ አይስማሙም። ያልተፈተነም እምነት አይሠራም። ለመሆኑ ምን ይሆን ያሳሰበው?

ለአብራም ሽልማቱና የልቡ ሙላት ከጠላት ያዳናቸው ሰዎች አድናቆትና ምሥጋና ሳይሆን የእግዚአብሔር አብሮት መሆን ለራሱ ሲረጋግጥለት ብቻ ነው።

ለአብራም ይሰማው የነበረው ፍርሃት አብሮት የቆየ ነው። ሁል ጊዜ እየተጉላላ የሚጠይቀው ጥያቄ አልተመለሰለትም፤ “… ጊዜዬ አልፏል፣ ከእንግዲህ ሊሆን አይችልም … በዚሁ ዓይነት እሞታለሁ” ይላል። ዘፍጥረት 1717

እግዚአብሔር አምላክ ግን የአብራምን ፍርሃት በሦስት መንገድ ይቆርጠዋል። የጌታ መልስ ደግሞ አያዳግምም።

አንደኛ፣ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን እወቅ።

  • ጋሻህ ነኝ። ዘፍ.151-
  • ሁሉን ቻይ ነኝ። ዘፍ.171-
  • ላንተና ለዘርህ ዕድል ፈንታህ ነኝ። ዘፍ.177-8

ሁለተኛ፣ የተናገርሁህን አስታውስ። ቃል ኪዳኔን አልረሳም፤ የተናገርሁትን አደርገዋለሁ። ዘፍጥረት 121-3። ስለዚህ፣

  • ወደ ራስህ አትመልከት። ምንም ጊዜ ቢሆን ወደ ራስህ ካየህ ተስፋ የለህም። ከውስጥህ ልብህ ይወድቃል። ትሸነፋለህ። አብራም እንዲህ የሚመስል ነገር ተናግሮ ነበርና፦ “… አረጀሁ፣ ዘመኔም ገሰገሰ፤ ከእንግዲህስ ምን ያህል ብኖር ወራሽ ልጅ አገኛለሁ? ሃብቴን ለቤቴ ሎሌ ጥዬ ስሜን የሚያስጠራ ሳይኖረኝ እሞታለሁ”። ዘፍጥረት 151-3
  • ወደ ሎሌህ አትመልከት። “… ኤልዔዘር ከኔ ይሻላል፤ በዕድሜም ጐልማሳ ነው፤ ምናልባት እግዚአብሔር ይህን ሰው ሊጠቀምበት ይችል ይሆናል እንጂ እኔንስ አይደለም” ብሎአልና። አዬ አብራም! ማንም ቢሆን እኰ እግዚአብሔር ካላሰበው አይረባም!! ሰው ደግሞ ወደ ራሱ ካየ ተስፋ የለውም፤ ወደ ሌሎች ሰዎችም ቢመለከት ተስፋ የላቸውም፤ ተስፋ አይሆኑም። ዘፍጥረት 153
  • ይልቅ “… ወደ ሰማይ ተመልከት፤ ክዋክብትን ልትቆጥራቸው ትችል እንደሆነ ቁጠር፤ ዘርህም እንደዚሁ ይሆናል”። ዘፍጥረት 155

ሁሉ ነገር ባዶ ሲሆንበት ሰው ሁሉ እግዚአብሔር ወደ አለበት ሠፈር ቢመለከት ተስፋ አለው። በጌታ ዙሪያ ብዙ መልካም ነገር አለና። ከፍርሃታችን የምናመልጥበት መንገድ ይኸው ብቻ ነው። ደግሞም ልክ ነው። እምነትም የሚኖረን ይኼኔ ነው!

ሦስተኛ፣ የተናገርሁህን እንደምፈጽመው ዕወቅ። እግዚአብሔር የተናገረውን በቃል ኪዳን ያጸናዋል። መያዣ ያበጅለታል። በአብራም ዘመን ታርደው ሥጋቸው በተከፋፈለ እንስሣት መካከል ማለፍ የስምምነት ወይም የቃል ኪዳን ምልክት ነበረ። በዚህ በኛ ዘመን በጽሑፍና በምስክር ፊርማ እንደሚጸና በዚያ ዘመን በደም ይጸና ነበር። ዘፍጥረት 159-21

የተበታተነውን የውል ሃሳብ ማን በራሱ ሊያይዘው ይችላል? እንዴትስ ይገጣጠም ይሆን? የቃል ኪዳናችን ዋነኛ ሰው፣ ምስክርና ኃላፊም እግዚአብሔር ነው። እርሱ የተበታተነውን መሰብሰብ አይቻለውምን? የተቆራረጠውንስ ማገጣጠም የርሱ ሥልጣን አይደለምን?

እግዚአብሔር አምላክ ይዋሽ ዘንድ ሰው አይደለም። የተናገረውን ይፈጽመው ዘንድ ለቃሉ ይተጋል። ነገር ግን የጌታን ጊዜ ማን ያውቀዋል? ቢሆንም እርሱ ሁሉን በሰዓቱ ውብ አድርጐ ይሠራዋል። ትንቢተ ኤርምያስ 112

§

 

 

picture