ርዕሰ አንቀጽ       

እ ን ዳ ይ ዛ መ ትእንዳይጋነን

ሰሞኑን በጂማ አካባቢ የታየው ግጭት ሊያሳስበን ይገባል። የዜና አውታሮች እንደ ዘገቡት ከሆነ ከክርስቲያኑና ከእስላሙ ወገን 15 ሰዎች ሞተዋል፤ የኦርቶዶክስ፣ የወንጌላውያንና የካቶሊክ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል። ችግሩ እንዳይዛመት ምን እርምጃ ይወሰድ የሚለው ነጥብ ሊያነጋግረን ይገባል።

በመሠረቱ አለመግባባት የሚፈጠረው መተማመን ሲጠፋ ነው። መተማመን ደግሞ የሚኖረው በጋራ ጉዳዮች ላይ ተቀራርቦ በመወያየት ነው። በዚህ ሁሉ ግን የግለሰቦችን ሚና ማስታወስ ይበጃል። ግለሰቦች ከእምነታቸው ጋር ፈጽሞ ባልተያያዘ ምክንያት ሊጣሉና ኋላም ተባባሪ ለማግኘት በሃይማኖት ሊያሳብቡ ይችላሉ። ወይም የሌላውን ልማድ የሚያንቋሽሽና ወደ ጠብ የሚወስድ ቃል ይለወዋጣሉ። ላለመተማመን ምክንያት የሚሆኑ ግለሰቦች የትኛውንም የእምነት ክፍል አይወክሉም፤ እንደሚወክሉም ተደርጐ መታሰብ የለበትም።

አንዳንዴም ለአካባቢው እንግዳ የሆነና የሚከፋፍል ዓላማ ያላቸው ኃይላት አለመግባባትን ይፈጥራሉ፤ ያባብሳሉ። የመንግሥት ድርሻ ባፋጣኝ ጠቡን ማስቆምና ማረጋጋት ሲሆን፣ ተቀራርቦ ጉዳዩን ማጣራትና ችግሩ እንዳይደገም መፍትሔ መሻት በቅድሚያ የሃይማኖት መሪዎች ኃላፊነት ነው።

አሁን የተከሰተው ጉዳይ ተጣርቶ ሕጋዊ እርምጃ ሲወሰድ የሃይማኖት ክፍሉን ሳይሆን የሚመለከተው በረብሻው ተባባሪ ሆነው የተገኙትን ሰዎች ብቻ ይሆናል።

በተጨማሪ ዜናውን ከማጋነን መቆጠብ ያስፈልጋል። ይህን የመሰለ ጥፋት በየወቅቱ መከሠቱ አልቀረም። ለአሁኑ ችግሩ የታየው በተወሰኑ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ከተሞች ነው። በመላ ኢትዮጵያ የሃይማኖት ግጭት እንደ ተቀጣጠለ ወይም በክርስቲያኑና በእስላሙ መካከል እልቂት እንደሆነ ተደርጐ ሊታሰብ ወይም ሊነገር አይገባም። የተሳሳተ አስተሳሰብ ለተሳሳተ ድርጊት ሁኔታን ያመቻቻልና። ይልቅ ለአገራችን ልማት በጐ ምኞት ያላቸው ሁሉ መጸለይና መግባባት እንዲገኝ መጣር ይጠበቅባቸዋል።

10/18/2005