ርዕሰ አንቀጽ

 

የጥበብና የሰላም መጀመሪያ ዛሬም እግዚአብሔርን መፍራት ነው

ሃይማኖት የጠብና የጦርነት መንስዔ ነው አፅንቶ መባል ከጀመረ ይኸው መቶ ዓመት አለፈው።

ሃይማኖት አክራሪነትን ያጸናል፤ የዓለማትን ታሪክ

  • በጐና ክፉ
  • ብርሃንና ጨለማ
  • ጽድቅና ኩነኔ፣ እያለ ይመድባል።

ለድርድር ሥፍራ የለውም፤ ቅራኔን ያሰፋል፤ ወደ ጠብ ያመራል፤ ይሉናል።

ስለ ሕይወት፣ ስለ ጽድቅ፣ ስለ እውነት “እርግጠኛ መሆን ይቻላል” ስለሚል በሰላም አብሮ መኖር እንዳይቻል ጋሬጣ ሆኗል።

ለዚህ መፍትኄው ሃይማኖትን ችላ ማለት ነው፣ ይሉናል።

ሰው መረን እንዳይወጣ፣ ከአራዊት እንዲለይ ሃይማኖት ያበረከተውን ሥነ ምግባርና ገደብ እነዚሁ ይዘነጋሉ፤ ማስታወስ አይፈቅዱም።

እርግጥ በሃይማኖት ስም በደል አልተፈጸመም አንልም። ሕዝብን ለማነሳሳት ሃይማኖታዊ ሽፋን አልተበጀም አንልም።

እውን ግን ሃይማኖት ለሰላም መጥፋት ምክንያት ነው?

የታሪክ ማኅደር ሲገለጥ በተለይ በሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን የታየው አሣር መነሻው ሃይማኖታዊ ሳይሆን ብሄራዊ፣ ፖለቲካዊና ኤኰኖሚያዊ ሆኖ እናገኘዋለን።

የሶቭየት ኅብረቱ ጆዘፍ ስታሊን ብቻውን ከሃያ ሚሊዮን ያላነሰ ሰው አስፈጅቷል። በዚህ ላይ የመጀመሪያውን የዓለም ጦርነት ይጨምሩ፣

·        ሁለተኛውን ይድገሙ።

·        የእስራኤልና የፍልስጤምስ?

·        የኰሪያ ጦርነት ለምን ይረሣ?

·        ቪየትናምስ?

·        የቻይና ሽብርና የባሕል አብዮት?

·        የኢትዮጵያስ የ 6/66 ግርግር?

·        የኢትዮጵያና የኤርትራ ውጊያ

·        ሩዋንዳ-ቡሩንዲ

·        ኰንጎ፣ ወዘተ

የአንዳቸውም መንስዔ ሃይማኖት እንዳልሆነ እንረዳለን።

እኛ ግን የጦርነት ምክንያት ሰው የራሱን ክብር መፈላለጉና ፈሪሃ እግዚአብሔር መጥፋቱ ነው እንላለን። አያቶቻችንና አባቶቻችን ሲጠሩት የኖሩት አምላክ መረሣቱ ነው፤ ችግሩ ያለው የሰው ልብ ጋ ነው፣ እንላለን፤

ከልብ ክፉ አሳብ፣ መግደል፣ ምንዝርነት፣ ዝሙት፣ መስረቅ፣ በውሸት መመስከር፣ ስድብ ይወጣልና (ማቴዎስ ወንጌል 15፡ 19)

· · ·

ፈሪሃ እግዚአብሔር ሲጠፋ ወጣቱ ለአዛውንቱ ከተቀመጠበት አይነሳም። ነጋዴው በሚዛን ይበድላል። የአገር መሪው ለሕዝብ አይራራም። ልጅ ወላጁን ያዋርዳል። ወልዶ ይጥላል፣ ችላ ይላል። ጫማ አስጠርጐ ጥፊ ይከፍላል፣ ካልቾ ይመርቃል። ሰውን በቋንቋና በቁመና ያገላል ወይም ያቀርባል። በአደባባይ ለሴቶች መብት ይከራከራል፤ ቤት ገብቶ ሚስቱን ያንገላታል።

ፈሪሃ እግዚአብሔር ሲጠፋ ጓዳው ከእግዚአብሔር ቤት ይበልጥበታል። ራሷን አላስደፍር ያለች ሴት ተማሪ ከትምህርት ገበታዋ ላይ ትፈናቀላለች። ይኸኛው ቃል ይገባል፣ ያፈርሳል። አማና ይበላል። ያኛው ፍቅረ-ንዋይን በረከት፣ ጮሌነቱን ጥሪ ይለዋል። መማለጃን የፍቅር ስጦታና መብት፣ የቡድን ስሜቱንና አንጀኛነቱን ደግሞ አንድነትና ኅብረት ብሎ ይሰይማቸዋል።

ፈሪሃ እግዚአብሔር ሲጎድል ምሑሩ ለእውነት አልገዛ ይላል። አብሮ የኖረ ወዳጅ ይከዳል። ሸክም ያንገላታት አህያ ዱላ ይጨመርላታል። ሕግ የሚያስከብረው ይሰርቃል። ቄሱ ያታልላል። ሐኪሙ ቃለ መሃላውን ያፈርሳል። ፈላስፋው፦ አመጽም እኰ ወደ ጽድቅ ያደርሳል ይላል።

· · ·

ፈጣሪ እንግዲህ አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ ነው። ፍጡር ደግሞ ዓለማት፣ ሰውና የሰው ሥራ ውጤቶች ናቸው። ፍጡር ፈጣሪውን ማምለክና በሥርዓቱ መተዳደር ድርሻው ነው።

ሰው ሳያመልክ መኖር አይችልም። ፈጣሪውን ካላመለከ ራሱን ያመልካል ወይም ተመልሶ ለገዛ እጁ ሥራ ይሰግዳል።

ለፈጣሪው የተለየውን የሕይወቱን ክፍል በተለያዩ ተግባራትና የኑሮ እንቅስቃሴዎች መሙላት ይሞክራል፤ ግን አይረካም። ለአምላክ ሥፍራ እስከሚለቅለት ድረስ ዕረፍትን አያይም። ይህን እውነት መፋቅ አይቻልም።

ፍጡር የፈጣሪን ሥፍራ ሲይዝ፣ ሁሉን መቆጣጠር ሲሻ፣ ያኔ ማኅበራዊ ቀውስ ይከተላል። ይኸ የዓለም ሕዝቦች ጥንትም ሆነ ዛሬ የሚያልፉበት የተመሰከረ ታሪካቸው ነው። ኃጢአት በመሠረቱ እግዚአብሔርን፦ “አታስፈልገኝም፣ እኔ በራሴ ብቁ ነኝ” ማለት ነው። ኃጢአት ከእግዚአብሔር መሸሽ ነው፤ ወደ መቅበዝበዝ ወደ ፍርሓትና ወደ ሞት ክልል ማዝገም ነው።

ወደ እግዚአብሔር መሸሽ ግን ጽድቅና ሰላም ሕይወትም ነው።

የኤኰኖሚ ስልት የሰው አዕምሮ ውጤት ነው፣ ስለዚህም ፍጡር ነው። አዕምሮ የተሰጠን ለምድራዊ ኑሮአችን እንድናውቅበት እንጂ ሰጭውን እንድንዘነጋበትና እርስ በርስ እንድንናናቅበት አይደለም። እውቀታችን የማኅበረ ሰብን ኅልውና መቆጣጠር ሲጀምር ለፈጣሪ የሚገባውን ቦታ ይዟልና አምላክ ሆነ ማለት ነው። ሰው አምልኰውን ወደ ፈጣሪው ሳይሆን ወደ ራሱ ሲያቀና በዚያው ልክ በስነ ልቡናውና በማኅበራዊ ግንኙነቱ ላይ ቀውስ መታየት ይጀምራል።

የኤኰኖሚ ሥርዓት ምን ያህል ቢሠምር በአምላክ ልክ የሰውን ሁለንተናዊ ፍላጐት ሊያረካ አይችልም። አሜሪካኖች ይመስክሩ። ጃፓኖችም ይጠሩ። ሰው ለእግዚአብሔር እንጂ እዕርሕሐሔሕሐሔ   

ለእንጀራ አልተፈጠረም፤ በእንጀራ ብቻ አይኖርም። ፍላጐቱ ከእንጀራ የሰፋና የጠለቀ ነው። የሰውን ኅልውናዊ ፍላጐት የሚያውቅለትና ፈጽሞ ሊሞላለት የሚችል አሁንም ፈጣሪው ብቻ ነው።

ፍላጐትን ደግሞ እንደ ኤኰኖሚ ሥርዓት መቀየስ አይቻልም፤ ዘመን ሲለዋወጥ ስሜትም ትውልድም መለዋወጡ አይቀርምና። ማኅበራዊ ድንጋጌዎች ብቻቸውን ውስጣዊ ማንነትን ሊያረኩ አይችሉምና። ስለዚህም ሰው ሌላ ይሻል፤ ያምጻል።

የኤኰኖሚው ስልት ኅብር ወዳድ ወይም ግለኛነትን የሚያገንን ይሆናል። ኅብር ወዳዱ ግላዊነትን ስለሚጫነው ፍጥጫ ይጀመራል። ፍጥጫው ወደ ማኅበራዊ አብዮት ይቀየርና የነበረውን ይሽረዋል።

የሰው ታሪክ ጐዳናው ፏፏ የሚባልበት ጥርጊያ ሳይሆን ባልተብላሉና በተፈረካከሱ ማኅበራዊ ፍልስፍናዎች የሰረጓጐጠ ነው። 

በሶቪየት ኅብረት ለሰባ ዓመት የሶሻሊዝም ሥርዓት አምላክ ሆኖ ሲያስገብር ኖረ። ሶሻሊዝም

ፍጡር ነው። የሰው አዕምሮ ውጤት ነው። ጅማሬው ተስፋና ፍትሕ እንዳለ የሚለፍፍ በመሆኑ ይማርካል፣ ያዘናጋል። ሌላ ይሆናል ብሎ አያስጠረጥርም። ፍጻሜውን ከጅምሩ ማወቅ አይቻልም ነበር ማለት ነው።

ከአምላክ ተነጥሎ ኑሮ ድንግዝግዝና ዳበሳ ነው። ሶሻሊዝም የፈጣሪን ቦታ ይዞ ኖረ። በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ንብረትና ሕይወት ተሰዋለት። ከባሕር የጠለቀ ዕንባ ረገፈለት። ካፒታሊዝም የሚባል ሌላ አምላክ ደርሶ አንኰታኰተው።

ሶሻሊዝም እኛም አገር ለአስራ ሰባት ዓመት አንገላታን። በጐሣ ፖለቲካ ተተካ። የጐሣ ፖለቲካ እንደ ቀደመው ሥርዓት ፍጡር ነው። ሰዎች የቀመሙት ነው። ያለ ፈሪሃ እግዚአብሔር የቀመሩት ነው። ሰው ከፈጣሪው ላይ ዓይኑን አንስቶ ፍጡር በሆነው ላይ አደረገ። ራሱንና ጐሣውን አስበለጠ። ራሱን ከሌላው ጋር አስተያየ፤ ሌላውን ናቀ። ከዚህም የተነሳ በወዳጆች መካከል ጠብና ጉስቁልና ነገሠ።

ካፒታሊዝም ሌላ ፍጡር ነው። የሰውን ቀማኛነት ይቀሰቅሳል፣ ያንጻል። ሰው በተፈጥሮው ንፉግ ነው፣ ራስ ወዳድ ነው። ይህን ባሕርዩን ሕጋዊ ዕውቅና ያጐናጽፈውና ያንቀሳቅስዋል። ፉክክር ያይላል፤ አብሮ ተጋርቶ መኖር ይዳከማል። በዚያው መጠን የኑሮ ልዩነት እየጐላ ይሄዳል።

የሶሻሊዝም አዝማሚያው ብዙሃንን እኩል ማደህየት ነው። የካፒታሊዝም ደግሞ ጥቂቶችን ማቅበጥ ነው። ይህን ለማቃናት ማኅበረ ሰቡ መነቃነቅ ይጀምራል፤ ሲያስፈልግም ያምጻል።

ሌላም ስም ያለው ቢኖር ያው የአዕምሮ ጥበብ ፍጡር ነው። ሁሉን በአዕምሮ ብርታት መፍታት ይቻላል ይላል። ገደብ እንዳለ ይዘነጋል። ትሕትና ይጐድለዋል፤ የትዕቢት መንገድ ነው።

ብዙ ሳይቆይ መፍታት የማይችለውም እንዳለ መገንዘብ ይጀምራል። ብዙ ካበላሸ በኋላ ማለት ነው። ላለመረታት፣ እጅ ላለመስጠት ይታገላል።

እግዚአብሔርን መፍራት ክብር እንጂ ውርደት እንዳልሆነ አይገነዘብም። ሙሉነት እንጂ ጉድለት እንዳልሆነ አያስብም። የመከባበሪያ ጐዳና እንደ ሆነ አያይም። የሰዎችን በደል በእግዚአብሔር ያላክካል። የሰዎችን በደል ሲኰንን እግዚአብሔርንም አብሮ ይኰንናል። ሰው መሆኑን፣ በሌሎች ላይ ያየው ጉድለት የርሱም ዕጣ መሆኑን ይክዳል።

እምነትና እውቀት እንደማይቃረኑ፣ እንዲያውም እንደሚጠባበቁ ይዘነጋል።

በሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ ላይ በሳይንስ ጥበብ ለሰው የሚጠቅሙ ብዙ ግኝቶች በጊዜው ለነበሩትና ዛሬም ላለነው የተስፋ ጮራ ፈንጥቋል። ለምሳሌ፦ ፔኒሲሊን ለብዙ ስውር ቀሳፊዎች መፍትሔ አስገኝቷል። ትንሽ ነች የምንላት አስፕሪን እንኳ በመቶ ዓመት ዕድሜዋ ስንቱን ራስ ምታትና ቁርጥማት ፈንግላለች። ስንት ፍላትና ትኩሳት አብርዳለች። ባጭሩ፣ እነዚህና የመሳሰሉት ግኝቶች ለኑሮ ቅልጥፍናን አስገኝተዋል።

አንዱን ችግር መፍታት ግን ሁሉን መፍታት ይመስለውና ሰው ይታለላል። እንደ ልጅ ቸኩሎ በጥቂቱ ይፈነድቃል። ጽኑ ተስፋና እምነት ካልተጨመረበት በስተቀር ነገ እንደሚያታግለው አያስብም። የሰው ሕይወት ብርቱ ሰልፍ ነው የተባለው ለዚህ ነው።

ሰው የራሱ ተስፋ ሰጭ ሊሆን አይችልም። የተገባው አይደለምና። አምላክ አይደለምና። ተስፋ ሰጭ ያለው ከሰው ውጭ ነው፤ እግዚአብሔር ብቻ ነው።

በጥበብ የገሰገሱት ለምድር ሁሉ መሪና ሚዛን አድርገው ራሳቸውን በአምላክነት ሾሙ። ወደዚህ የሥልጣኔ ደረጃ ያልደረሱትን ማስገበር መግዛት ፈለጉ። ሁሉም በተገኘበት ከበታቹ ያለውን ማንበርከክ ተግባሩ ሆነ። ራሱን ማግነን ለሰው የማያቋርጥ ምኞቱ ሆነ። ከአምላክ ሥልጣን በታች መሆኑን ዘነጋ።

ለፈጣሪ የሚገባውን ክብር ለአዕምሮው ውጤት፣ ለሥልጣኔውና ለወገኑ ክብር አዋለ። ከዚህ የተነሣ ዘላቂ የሆነ ስምምነት ሊገኝ አልቻለም። ራስን ማግነን ድሮም ቢሆን ውጤቱ ከዚህ አያልፍም። ቅድም እንዳመለከትነው መቆራቆስና ምድርን ማወክ ተጀመረ። ሰው ራሱን ስላነገሠና ሌላው ሁሉ እንዲሰግድለት ስለሻ ብዙ ቀውስ ተከተለ።

በዚህም የሰው አዕምሮ ብቻውን ሁሉን ቻይ አለመሆኑን በራሱ ላይ መሰከረ።

የሰው ብልሃት የፈጣሪን ሥርዓት አይቀይርም። የፈጣሪን ሥርዓት የሚቀይር ተአምር ብቻ ነው፤ እግዚአብሔር ብቻ ነው። ተአምር የማድረግ ሥልጣን ደግሞ ለአምላክ እንጂ ለሥጋ ለባሽ አልተሰጠም።

የሰው ብርታት የአምላክን ድካም አይረታም። አምላክ ድካም አለው ከተባለ ማለት ነው። የጥበብና የሰላም መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው። የራስን ክብር መፈላለግ ዛሬም እንደ ጥንቱ የውድቀት መጀመሪያ ነው:: ራስን ማክበር እግዚአብሔርን አለመፍራት ነው፤ ሰውን መናቅ ነው። ራሳቸውን የሚያከብሩ ይዋረዳሉ፤ ለከንቱነትም አልፈው ይሰጣሉ።

*    *    *    *    *

የሰማነውን ነገር ማን አምኖአል?

 

የእግዚአብሔርስ ክንድ ለማን ተገልጦአል? በፊቱ እንደ ቡቃያ ከደረቅም መሬት እንደ ሥር አድጎአል። መልክና ውበት የለውም፥ ባየነውም ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም። የተናቀ ከሰውም የተጠላ፥ የሕማም ሰው ደዌንም የሚያውቅ ነው፤ ሰውም ፊቱን እንደሚሰውርበት የተናቀ ነው፥ እኛም አላከበርነውም። በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ ሕመማችንንም ተሸክሞአል፤ እኛ ግን እንደ ተመታ በእግዚአብሔርም እንደ ተቀሠፈ እንደ ተቸገረም ቈጠርነው። እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን። እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ፤ እግዚአብሔርም የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ። ተጨነቀ ተሣቀየም አፉንም አልከፈተም፤ ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም። በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ፤ ስለ ሕዝቤ ኃጢአት ተመትቶ ከሕያዋን ምድር እንደ ተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ? ከክፉዎችም ጋር መቃብሩን አደረጉ፥ ከባለጠጎችም ጋር በሞቱ ሆኖም ግፍን አላደረገም ነበር፥ በአፉም ተንኮል አልተገኘበትም ነበር። እግዚአብሔርም በደዌ ያደቅቀው ዘንድ ፈከደ፤ ነፍሱን ስለ ኃጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል፥ ዕድሜውም ይረዝማል፥ የእግዚአብሔርም ፈቃድ በእጁ ይከናወናል። ከነፍሱ ድካም ብርሃን ያያል ደስም ይለዋል፤ ጻድቅ ባሪያዬም በእውቀቱ ብዙ ሰዎችን ያጸድቃል፥ ኃጢአታቸውን ይሰከማል። ስለዚህም እርሱ ብዙዎችን ይወርሳል፥ ከኃያላንም ጋር ምርኮን ይከፋፈላል፤ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአልና፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና፤ እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ … 

ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና። ስለ ጻድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና፤ ስለ ቸር ሰው ግን ሊሞት እንኳ የሚደፍር ምናልባት ይገኝ ይሆናል። ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን። ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን፤ ይህም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን አሁን መታረቁን ባገኘንበት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በእግዚአብሔር ደግሞ እንመካለን። ስለዚህ ምክንያት ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፥ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ፤ ሕግ እስከ መጣ ድረስ ኃጢአት በዓለም ነበረና ነገር ግን ሕግ በሌለበት ጊዜ ኃጢአት አይቈጠርም፤ ነገር ግን በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ኃጢአትን ባልሠሩት ላይ እንኳ፥ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ፤ አዳም ይመጣ ዘንድ ላለው ለእርሱ አምሳሉ ነውና። ነገር ግን ስጦታው እንደ በደሉ መጠን እንደዚያው አይደለም፤ በአንድ ሰው በደል ብዙዎቹ ሞተዋልና፥ ነገር ግን የእግዚአብሔር ጸጋና በአንድ ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የሆነው ስጦታ ከዚያ ይልቅ ለብዙዎች በዛ። አንድ ሰውም ኃጢአትን በማድረጉ እንደ ሆነው መጠን እንደዚያው ስጦታው አይደለም፤ ፍርድ ከአንድ ሰው ለኵነኔ መጥቶአልና፥ ስጦታው ግን በብዙ በደል ለማጽደቅ መጣ። በአንዱም በደል ሞት በአንዱ በኩል ከነገሠ፥ ይልቁን የጸጋን ብዛትና የጽድቅን ስጦታ ብዛት የሚቀበሉ በአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሕይወት ይነግሣሉ። እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኵነኔ ወደ ሰው ሁሉ እንደ መጣ፥ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ ምክንያት ስጦታው ሕይወትን ለማጽደቅ ወደ ሰው ሁሉ መጣ። በአንዱ ሰው አለመታዘዝ ብዙዎች ኃጢአተኞች እንደ ሆኑ፥ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች ጻድቃን ይሆናሉ። በደልም እንዲበዛ ሕግ ጭምር ገባ፤ ዳሩ ግን ኃጢአት በበዛበት፥ ኃጢአት በሞት እንደ ነገሠ፥ እንዲሁ ደግሞ ጸጋ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተነሣ በጽድቅ ምክንያት ለዘላለም ሕይወት ይነግሥ ዘንድ፥ ጸጋ ከመጠን ይልቅ በለጠ …

ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው። ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ይገባዋል። በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና። ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና። በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል። ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው። ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል …

በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችሁ፤ በእነርሱም፥ በዚህ ዓለም እንዳለው ኑሮ፥ በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደ ሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ፥ በፊት ተመላለሳችሁባቸው። በእነዚህም ልጆች መካከል እኛ ሁላችን ደግሞ፥ የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን እንደ ሌሎቹም ደግሞ ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን። ነገር ግን እግዚአብሔር በምሕረቱ ባለ ጠጋ ስለ ሆነ፥ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና፥ በሚመጡ ዘመናትም በክርስቶስ ኢየሱስ ለእኛ ባለው ቸርነት ከሁሉ የሚበልጠውን የጸጋውን ባለ ጠግነት ያሳይ ዘንድ፥ ከእርሱ ጋር አስነሣን በክርስቶስ ኢየሱስም በሰማያዊ ስፍራ ከእርሱ ጋር አስቀመጠን።

ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤ ማንም እንዳይመካ ከሥራ አይደለም። እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን። ስለዚህ እናንተ አስቀድሞ በሥጋ አሕዛብ የነበራችሁ፥ በሥጋ በእጅ የተገረዙ በተባሉት ያልተገረዙ የተባላችሁ፥ ይህን አስቡ፤ በዚያ ዘመን ከእስራኤል መንግሥት ርቃችሁ ለተስፋውም ቃል ኪዳን እንግዶች ሆናችሁ በዚህም ዓለም ተስፋን አጥታችሁ ከእግዚአብሔርም ተለይታችሁ ያለ ክርስቶስ ነበራችሁ። አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ በክርስቶስ ደም ቀርባችኋል። እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፥ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው። መጥቶም ርቃችሁ ለነበራችሁ ለእናንተ ሰላምን፥ ቀርበው ለነበሩትም ሰላምን የምስራች ብሎ ሰበከ፤ በእርሱ ሥራ ሁላችን በአንድ መንፈስ ወደ አብ መግባት አለንና። እንግዲያስ ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም። በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፥ የማዕዘኑም ራስ ድንጋይ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፤ በእርሱም ሕንጻ ሁሉ እየተጋጠመ በጌታ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንዲሆን ያድጋል፤ በእርሱም እናንተ ደግሞ ለእግዚአብሔር መኖሪያ ለመሆን በመንፈስ አብራችሁ ትሠራላችሁ።

ኢሳይያስ 53፡ 1-12፤ ሮሜ 5፡ 6-21፤ ዮሐንስ 3፡ 13-21፤ ኤፌሶን 2፡ 1-22፤

Top art credit: www.stailbe.org

 

 

 

 

 

Copyright © 2006 ethiopianchurch.org