የክርስቶስ ተከታዮች በግልም ሆነ በማኅበር በዓለም ውስጥ ናቸው፤ ከዓለም ግን አይደሉም። ዓለምን በወንጌል ስብከት ሊለውጡ እንጂ በዓለም ሊለወጡ አይጠበቅባቸውም [ዮሐንስ 17፡14-19። ሮሜ 12፡1-2]። ቤተክርስቲያን አንዴ በምድራዊ ሥልጣን ዙሪያ ስትወዛገብና ከሥልጣናት ጋር ስትወሳሰብ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ምድራዊውን ጨርሶ ስትዘነጋ ታይታለች። እንደ መሪዎቿ አስተዋይነትና ለዘብተኛነት ጠቃሚና ጎጂ የሆኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ውጤቶችንም አስመዝግባለች። ለምሳሌ፣ በ1980ዎቹ አጋማሽ ጨቋኝ አገዛዞችን ለመገርሰስ በፖላንድና በሃንጋሪ የተቀጣጠለው የነጻነት ችቦ የተለኮሰው በ[ካቶሊካዊት] ቤተክርስቲያን ነበር። ቤተክርስቲያን ማኅበረሰባዊ ድርሻዋ እስከምን ድረስ ነው? ፖለቲካ ምንድነው? መንፈሳዊነትስ? ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ ናቸው፤ አንዱ በሌላው ጉዳይ ጣልቃ አይገባም ሲል ምን ማለቱ ነው? ከዓለማዊ አኗኗርና አሠራር የተለዩ ሆኖ የክርስቶስን ማኅበር ዓይነተኛነት በዓለም ላሉት እንደ ዘላቂ አማራጭ ለማቅረብ እንዴት ይቻላል? የቤተክርስቲያን ተቀዳሚ ተልእኮ ምንድነው? አማንያን በግልና በማኅበር ምስክርነታቸው እንዳይጎድፍ ምን ጥንቃቄ ይውሰዱ? ቤተክርስቲያንስ እንደ አንድ ድርጅት በወቅቱ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፏና ማኅበረ ምእመኗን ማሳተፏ ተገቢ ነው? በፖለቲካ ቀጥተኛ ተሳትፎ ማድረግ ለሁሉም ይሆናል ወይ? ከወንጌል እውነትና ከፍትኅ ጋር መቆምና መራመድ ማለት ምን ማለት ነው? እነዚህ ዋነኛና አነጋጋሪ ጥያቄዎች ናቸው። ወንድም ተስፋዬ ሮበሌ አንዱን አመለካከት ይዞልን ቀርቧል። በቀረበው ጽሑፍ ላይ ተጨማሪ ወይም የተለየ አሳብ ካላችሁ በ”ወርድ” ፋይል በ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ላኩልን። ከአዘጋጁ።

ክርስቲያን በፖለቲካ ውስጥ በንቃት መሳተፍ ይኖርበታልን?

­­­በተስፋዬ ሮበሌ

በአንድ መስቀለኛ መንገድ ላይ በየቀኑ አሠቃቂ አደጋ ይከሠታል፤ ከአደጋው የተነሣም በርካታ ሰዎች ይሞታሉ፤ ከፍተኛ ንብረትም ይወድማል። ሁኔታው ያሳሰባት፣ በዚህ አካባቢ የምትገኝ አንዲት ቤተ ክርስቲያን፣ የአደጋውሰለባ የሆኑትን ሰዎች የሚረዱ ሐኪሞችንና ነርሶችን በማሠማራት የአካባቢውን ማኅበረሰብ በንቃት ማገልገሉን ሥራዬ ብላ ተያያዘችው። የሕዝብና የመኪና ቊጥር ዕለት በዕለት እየጨመረ በመሄዱ ምክንያት ግን፣ ችግሩ በዛውመጠን ተባብሶ ቀጠለ። ይህች ቤተ ክርስቲያን እርዳታዋን በመጠንና በዐይነት ማሳደግ ብቻ ሳይሆን፣ አንድ መለስተኛ ሆስፒታል አደጋው በሚከሠትበት አካባቢ አቋቋመች። ይህ ሠናይ ምግባር የሰለባዎቹን ጤንነትና ሕይወትከመታደግ አንጻር ብዙ ጠቀሜታ ቢኖረውም፣ ችግሩን ግን ከምንጩ ማድረቅ አልቻለም። ምክንያቱም የችግሩ ምንጭ የተሳሳተ የመንገድ ቅያስ ነውና። በመስኩ የሠለጠኑ መሐንዲሶች መንገዱን በአዲስ መልክ ቢሠሩ ችግሩ ሊፈታ እንደሚችል የትራፊክ ፖሊስ ጽሕፈት ቤቱን በቃልም ሆነ በጽሑፍ ቢያሳስቡም፣ ባልታወቀ ምክንያት ጽሕፈት ቤቱ ጆሮ ዳባ ልበስ አለ።

በየዘመናቱ ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስ ሰጠኝ የምትለውን ዐደራ ከዳር ለማድረስ፣ በሚያስፈልገው ሁሉ በመውተርተር ላይ ትገኛለች። ቤተ ክርስቲያን ነዳያንን በማብላት፣ የታመሙትን በማስታመም፣ ለመበለቶች ዳኛ በመሆንጥልቅ ስም አላት። በርግጥም ቤተ ክርስቲያን የምስካየ ሕዙናን መንበር ናት። ወደ ፊትም ይህንኑ ግብረ ሠናይ ምግባሯን አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት አያጠያይቅም። ነገር ግን ችግሩን በዘላቂነት መፍታት የምትችለው የተሳሳተፖሊሲ ያስከተለውን ፍሬ በመልቀም ብቻ ሳይሆን፣ መንግሥት ትክክለኛ ፖሊሲ እንዲነድፍ ስታሳስብ፣ መንግሥት ሲሳሳትም ስሕተቱን ስሕተት ነው ማለት ድፍረትና ክህሎት ሲኖራት ብቻ ነው።

ፖለቲካ፣ የሕዝብ አስተዳደር መዘውር ነው። ቤተ ክርስቲያን የመዘውሩ ነገር ምን ተዳዬ የምትል ከሆነ ግን፣ በመዘውሩ እክል ምክንያት በሚከሠቱ ችግሮች ላይ ብቻ መጠመዷ አይቀሬ ነው። ይህ አስተሳሰብ በክርስቲያኑማኅበረሰብ ውስጥ ሠርጾ በመዝለቁ ምክንያት፣ ወደ ፖለቲካው ዓለም የሚገቡ ወይም የፖለቲካ ሳይንስ የሚያጠኑ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ ከመንፈሳዊነት እንደ ጐደሉ ምናልባትም ክርስቶስን ከመከተል እንዳፈገፈጉ ይታሰባል።ክርስቲያን "የዓለም ብርሃን" ነው፣ "የዓለም ጨው" ነው የሚለው የቃለ እግዚአብሔር ትምህርት፣ በፖለቲካ ሕይወት ውስጥ ጨለማና አልጫ ነው ያለው ማነው? እንዲያውም ክርስቲያኖች በንቃት ሊሳተፉበት የሚገባ፣ጨውነታቸውንና ብርሃንነታቸውን ሊገልጡበት የሚገባው የሕይወት ክፍል ፖለቲካ ነው። እንደ ንጉሥ ዳዊት፣ እንደ ንጉሥ ሰሎሞን ያሉ የእምነት አበው ፖለቲከኞች ነበሩ። እንደ ነቢዩ ናታን፣ ነቢዩ ኢሳይያስ፣ ነቢዩ ዳንኤል፣ ነቢዩ አሞጽ ወዘተ ያሉ ነቢያት ደግሞ መንግሥትን በማማከር አገልግለው እንዳለፉ ገድላቸው ይናገራል። መንግሥት ሲስት ይገሥጹና ከስሕተቱ እንዲመለስ መንገድ ያመላክቱ እንደ ነበር ቅዱስ ቃሉ ያስተምረናል። እንዲያውም ባልንጀራህን/ጐረቤትህን እንደ ራስህ ውደድ የሚለው የክርስቶስ ቃል ከየትኛውም የትምህርት ዘርፍ ይልቅ ፖለቲካን የሚያመላክት ነው (ማቴዎስ 22÷39)። ለተጠቃው ከመጮኽ፣ የታረዘውን ከማልበስ፣ ፍትሕ ያጣውን ለፍትሑ ከመሟገት በላይ ምን ጐረቤትን መውደድ አለ? እግዚአብሔር አምላክ ለንጉሥ ሰሎሞን የሰጠው ስጦታ የፖለቲካ ስጦታ ነው። ይህ ደግሞ ፖለቲካ የጸጋ ስጦታ መሆኑን የሚያጸና ነው።

ወገኖቼ ክርስትና የማይዳስሰው የሕይወት ክፍል የለም። ክርስቲያኖች በፖለቲካው ውስጥ በመግባት ብርሃንና ጨው መሆን ካልቻሉ፣ ክርስቲያን ያልሆኑና እኵይ ሥነ ምግባር ያላቸው ሰዎች የፖለቲካውን መድረክመቈጣጠራቸው አይቀሬ ነው። እየሆነም ያለ ይመስላል። ወገኖቼ፣ "ኀጥኣን ከፍ ከፍ ሲሉ ሕዝብ ይጨነቃል" የሚለው የጠቢቡ ሰሎሞን አነጋገር ፖለቲካን ታሳቢ ያደረገ ነው። ወዲህም ወዲያም ብታገላብጡት ሐቁ ይኸውነው። ክርስትናና ፖለቲካ ዐይንና ናጫ ናቸው ወዘተረፈ የሚለው ወልጋዳ አስተሳሰብ የብዙዎችን ጐዳና አሰናክሏል። ከዚህም የተነሣ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ልጆች፣ ስለ ፖለቲካ ያለን ዕውቀት በየጋዜጣው ላይ ከሚጻፉመጣጥፎች እንዲሁም በየዜና አውታሮች ከሚተላለፉ ፕሮግራሞች የዘለለ አይደለም። ይህ ዐይነቱ ዕውቀት ደግሞ፣ ለፕሮፖጋንዳ ውዥንብር በቀላሉ ይዳረጋል። ቃላትን ቀምሮና እውነትን አስታኮ የመጣ ብልጣብልጥ ፖለቲከኛሁሉ ወዳሻው ቦታ ይዞት ይሄዳል። ወደድንም ጠላንም "የአገሬ ጕዳይ ግድ ይለኛል" የምንል ሰዎች ሁሉ፣ ቢያንስ መሠረታውያን የሚባሉትን የፖለቲካ መርሖች በቅጡ ልናውቃቸው ግድ ነው። ለምሳሌ ፖለቲካ በአገር ግንባታ ውስጥ ያለው ቦታ እስከምን ድረስ ነው? ሰብአዊ መብት ማለት ምን ማለት ነው? ኢሕአዴግ፣ "አብዮታዊ ዴሞክራሲ" ብሎ የሚጠራው የፖለቲካ አካሄድ፣ ከምዕራባውያኑ ለዘብተኛ (ሊበራል) ዴሞክራሲ በምን ይለያል? ይህ የፖለቲካ ፍልስፍና በአገሪቱ ፖለቲካና ምጣኔ ሀብት የሚያስከትለው አሉታዊ መዘዝም ሆነ አዎንታዊ እንድምታ እንዴት ይተነተናል? ክርስቲያኖች በፖለቲካ ውስጥ ተሳትፎ ማድረግ አለባቸው ወይስ የዳር ታዛቢ መሆናቸው ብቻ ጥሩ ዜጋ ያሰኛቸዋል? ሕዝባዊና ማኅበራዊ ተቋማት ማለትም የመገናኛ ብዙኃን፣ ፖሊስ፣ ፍርድ ቤቶችና የምርጫ ቦርድ "ከመንግሥት ጣልቃ ገብነት ፍጹም ነጻ መሆን አለባቸው" የሚባለው ለምንድን ነው? ነጻ ናቸው የሚባል ከሆነስ ደግሞ ነጻነታቸው በምን መስፈርት ይለካል? ፖለቲካ ለምጣኔ ሀብት ሕግጋት ይገዛል ወይስ ምጣኔ ሀብት ለፖለቲካ ሎሌ ያድራል? ወይስ ሁለቱም ለየቅል ናቸው? የአንድ አገር ፖለቲካ ሰብአዊ መብትን እንዳሻው እየጨፈለቀ የምጣኔ ሀብት በረከት ሊያመጣ ይችላል? የማይቻል ከሆነ የቻይና ጕዳይ እንዴት ይታያል? የመናገር መብት፣ የመጻፍ መብት፣ የመደራጀት መብት ወዘተ የሚባሉት ጕዳዮች፣ በሰብአውያን ሕይወትና ዕድገት ውስጥ ያላቸው ስፍራ ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፖለቲካ የሚያስተምረው ትምህርት ምንድንነው? አንድን የፖለቲካ ድርጅት ለመቃወም ሆነ ለመደገፍ የፖለቲካ ፕሮግራሙንና የሥነ ምግባር ሕጉን እንዴት መፈተሽ ይቻላል?

ቢያንስ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች እነዚህን ርእሰ ጕዳዮች በሚገባ ማወቅ አለብን። ቤተ ክርስቲያንም እነዚህን የፖለቲካ መሠረታውያንን ለአባሎችዋ በሚገባ ማስተማር ይኖርባታል። ቤተ ክርስቲያን ይህን የቤት ሥራዋንመሥራቷ በአገር ግንባታ ውስጥ ተሳትፎ ማድረጓ እንጂ፣ ሃይማኖት በፖለቲካ ውስጥ ጣልቃ መግባቱ ወይም ሃይማኖትንና ፖለቲካን "ማጣቀስ" አይደለም። ቤተ ክርስቲያን ልጆችዋን በሥርዐቱ የማታሠለጥን ከሆነ ሌሎችበተጣመመ መንገድ "ያሠለጥኑላታል"። ድሮስ ጨው ጨውነቱን ካጣ መረገጥ እንጂ ምን ዕድል ፈንታ አለው?

የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ዐቅም ባጡበት ጕዳይ ላይ ሒስ የሚሰነዝሩ፣ አቅጣጫን የሚያመለክቱ፣ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ከፖለቲካ ከጫወታ ውጪ ነኝ፤ አይመለከተኝም የሚል አስተሳሰብ እንዳያድርባቸው ቃለእግዚአብሔርን በመጥቀስ ወደ ጫወታው እንዲገቡ የሚሞክሩ ጸሐፍያን ያስፈልጉናል። "ቤተ ክርስቲያን ሆይ ተነሽ" የሚል ነቢያዊ ጩኸት የሚያሰሙ የቊርጥ ቀን ልጆች የሚያስፈልጉን ይመስለኛል። መቼም የቤተ ክርስቲያንመሪዎችን ሁሉ በአንድ መፈረጅ አግባብ ባይሆንም፣ አብዛኞቹ መሪዎቻችን ልፍስፍሶች መሆናቸውን እንኳን ምዕመናን እነርሱ ጭምር የሚስማሙበት ይመስለኛል። "አልታየሁም"፣ "አልታወቅም"፣ "ነውሬ ተረስቶአል"የሚሉ ካሉ ሞኞች ናቸው። ከታሪክ ዐይን የሚያመልጥ የለም። ይህ ግን እውን መሆኑን የሚያሳዩ ጸሓፍያን እንጠብቃለን—እውነትን በፍቅር የሚገልጹ።

አብዛኞቹ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች፣ መስሎ ለመኖር ብቻ ውሃና ዘይትን ካለዋሃድን፣ እሳትና ጭድን ከላፋቀርን፣ ዐይንና ናጫን ከላስማማን የሚል አቋም ያላቸው ይመስላል። እውነትን ከጥቃት የምንጠብቀው ሐሰትን በግልጥበመቃወም ጭምር ነው። በልፍስፍስ አቋሙ በባልንጀሮቹ በስፋት የሚታወቅ አንድ ወንድማችንን ሌላው ወንድማችን፣ "ክርስቶስ ሰምራ" ብሎ ይጠረዋል። አንድ ቀን፣ "ወዳጄን ዳቦ ሳትቈርስ 'ክርስቶስ ሰምራ' ብለህ ስምያወጣህለት ለምንድን ነው? ለመሆኑስ ክርስቶስ ሰምራ ማን ነች?" ስል ጠየቅሁት። "አታቅም እንዴ፣ ክርስቶስ ሰምራ የምትባል ክርስቶስንና ሰይጣንን ለማስታረቅ ሙከራ ያደረገች ብጽዕት ናት፤ እኔም ይህን ወንድም ከክርስቶስሰምራ ለይቼ አላየውም፤ ለመኖር ሲል ብቻ ሁሉም ትክክል ነው የሚል እርስ በርሱ የተምታታና የተውገረገረ አቋም ያለው ፍጥረት ነው" አለኝ በሐዘንና በቊጣ። በርግጥ ስያሜው ወዳጄን በትክክል እንደሚመጥነው እቀበላለሁ፤ ገላጩ ስያሜ ግን አስቆኛል።

መቼም መንግሥት ከእርሱ ተቃራኒ ዘዌ የቆሙትን ሁሉ "ጸረ" የሚል የመነሻ ምዕላድ እየቀጸለ፣ ጽንፍ የነካ በመሰለበት በዚህ የታሪክ ጊዜ፣ መለሳለስ ጥሩ ስልት መስሎ ሊታይ ይችል ይሆናል።ግን የክርስቶስ ወንጌል የጀግኖችመለዮ እንጂ፣ የአልጮች ሙያ አይደለምና ልፍስፍስ አቋማቸውን መቀየር የግድ ይኖርባቸዋል። ለዚህ ነው አንድ ወንድማችን ይህን አስመልክቶ፣ "አቋም የለሽ አቋማችን" እንዲስተካከል በአንድ ጽሑፉ የሚማጠነን። እውነትነው አቋም የለሽ አቋማችንን እክ እንትፍ እንበለው። የአቋም ሰው መሆን ያስከብር ከሆነ እንጂ አያዋርድም (ቢያንስ በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት)።