የብሔረሰቦች ጎሳዊ ትስስር ለማኅበረሰብ ሰላምና ለአገር አንድነት
ፕሮፌሰር ገብሬ ይንቲሶ ደኮ

የኢትዮጵያ ብሔሮችና ብሔረሰቦች በጥልቅ የጎሳ፣ የጋብቻና ሌሎች ማኅበራዊ መስተጋብሮች የተሳሰሩ ናቸው። የአንድ ጎሳ አባላት በተለያዩ ብሔረሰቦች ውስጥ መገኘት የተለመደ ነው። በአባት ከአንድ ብሔረሰብ በእናት ከሌላ የሆኑ ወይም የአያትና የቅድመ አያት የዝምድና ሐረግ ሲመዘዝ ደማቸው የብዙ ብሔረሰብ ውህድ የሆኑ ኢትዮጵያውያን ቁጥራቸው ብዙ ነው። ኢትዮጵያውያን ከቤተ ዘመድ፣ ከጎሳና ከብሔረሰብ ድንበር አልፈው የሚተሳሰሩበት በርካታ ባህላዊ መንገዶች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አበልጅ፣ ጉዲፈቻ፣ ጃላ እና በሊ (በላንቶ) ይገኙበታል። ደማዊ ግንኙነት ባይኖራቸውም መዋለድ ቋንቋ ነው ብለው የሥነ ልቡና አንድነት አዳበረው በአንድ ሰፈር ሐዘንና ደስታ እየተጋሩ በእኩልነት ስሜት ተፈቃቅደው በፍቅርና በሰላም የሚኖሩ ሕዝቦች ቁጥርም እንደዚሁ አያሌ ነው። ነገር ግን ራስወዳድነትና ቡድንተኝነት ከአስተውሎት ጉድለት እንዲሁም ከመረጃ ዕጥረት ጋር ተዳምረው የሕዝቦችን ነባር ትስስርና ትብብር ክፉኛ እየተፈታተኑ ይገኛል።

ኢትዮጵያ ውስጥ ከሰማንያ በላይ ብሔር/ብሔረሰቦች ይገኛሉ። አማራ፣ ትግራይና ሌሎች ጥቂት ብሔረሰቦች የጎሳ ሥርዓት ወይም አከፋፈል ባህል ባይኖራቸውም ኦሮሞ፣ ሶማሌና ሌሎች ብሔረሰቦች በሙሉ በጎሳ የተከፈፈሉ ናቸው። የብሔርና የጎሳ ልዩነት በመላው ዓለምና በአገራችን የነበረ፣ ያለና ለማይታወቅ ጊዜ የሚቀጥል ነው። በብሔረሰቦች መሀል ልዩነት ብቻ ሳይሆን ትስስርም መኖሩን ማወቅና ማሳወቅ የዜጎች ግዴታ ነው። ኢትዮጵያውያን በልዩነታቸው ውስጥ አንድነት፣ በአንድነታቸው ውስጥ ልዩነት የሚታይ በጎሳና በጋብቻ ሐረግ የተቆራኙ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው።

የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ከእውነታ በመነሳት በዘመናችን የሚስተዋለውን አንዳንድ የአረዳድ ብዥታዎች በማጥራት የብሔረሰቦች ትስስር እንዴት ለማኅበረሰብ ሰላምና ለአገር አንድነት ሚና እንዳለው ማሳየት ነው። በተለይም በብሔረሰቦች መሀል የነበረና ያለውን ጎሳዊ ትስስር እንደ ጠቃሚ ባህላዊ ዕሴት ማጉላት፣ የዘመኑን የመጠፋፋት አዝማሚያ በአስተውሎት ለማለፍና ለመጪው ትውልድ ያልተከፋፈለች አገር ለማስረከብ አስተዋጽኦ ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ።

የብሔረሰብ ማንነትን በተመለከተ የተለያዩ ዕሳቤዎችና ግንዛቤዎች አሉ። አንዱ ዕሳቤ ማንነት ቋሚና ዘላቂ ነው የሚል ሲሆን፣ የአንድ ብሔረሰብ አባላት ግንኙነት ደማዊ ወይም ተፈጥሮአዊ እንደሆነ ተደርጎ ይቀርባል። ይህ አቀራረብ አንዱ ብሔረሰብ ከሌላው ጋር የማይገናኝ አስመስሎ ያቀርባል። ሁለተኛው ዕሳቤ በውስጡ ልዩነት ቢኖረውም መነሻ ሐሳቡ ማንነት ቋሚና ዘላቂ ሳይሆን የሚለዋወጥ (የሚሰፋና የሚጠብ) እና እንደ አዲስ ሊከሰት የሚችል ነው የሚል ነው። ከዚህ ውጭ አገራዊ ማንነት ላይ በማተኮር ሌሎች ማንነቶችን የሚክዱ ወይም የማይቀበሉ ሰዎች አሉ። ፍላጎታቸውና ምኞታቸው እንደ አሜሪካ፣ ጀርመንና ሌሎች ያደጉ አገሮች የዜጎች ትኩረት አገራዊ ማንነት ላይ እንዲሆን ነው። ይህ የኔም ምኞት ቢሆንም ከአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር (የብሔር ማንነት ከሕዝቦች መብትና ጥቅም ጋር ስለተወሳሰበ) ብዝኃነትን ከመካድ ይልቅ የተቆራኘበትን ገመድ አውቆ ትስስሩን ማጠባበቅ ሕዝቦችን ለማቀራረብ ይረዳል።

የብሔረሰብ ማንነት ደማዊና ዘላቂ ነው ወይስ አይደለም ወደሚለው ሐሳብ ስንመለስ በኢሕአዴግ ዘመነ መንግሥትና ከዚያም በፊት የተከሰቱ ክስተቶችን መቃኘት ጠቃሚ ይሆናል። የጉራጌ ብሔረሰብ አካል ተደርጎ ይቆጠር የነበረው ስልጤ ዛሬ ራሱን የቻለ ብሔረሰብ መሆኑ ተረጋግጧል። የኛንጋቶም ብሔረሰብ አካል ተደርጎ ይቆጠር የነበረው ሙርሌም ዛሬ ራሱን የቻለ ብሔረሰብ ነው። የአማራ አካል ተደርጎ ይወሰድ የነበረው ቅማንት ብሔረሰባዊ ማንነቱ የተረጋገጠው በቅርብ ነው። ለረዥም ጊዜ እንደ ሁለት ብሔረሰብ ይቆጠሩ የነበሩት ገዋዳና ዶባሴ ሁለት ሳይሆኑ አንድ አሌ የሚባል ብሔረሰብ መሆኑ ከተረጋገጠ ብዙ አልቆየም። ባይሶ የሚባሉ የኩሽቲክ ቋንቋ ተናጋሪዎችና ሐሮ የሚባሉ የኦሞቲክ ቋንቋ ተናጋሪዎች ጊድቾ በሚል ስያሜ የብሔረሰብ ማንነት የተጎናፀፉትም እንደዚሁ በቅርብ ነው። ከሁለት ብሔረሰቦች ተውጣጥተው አንድ ብሔረሰብ የፈጠሩ ሌሎችም አሉ። የጋሪ ብሔረሰብ አብዛኛው ሶማሌ ሲሆን ቀሪው ኦሮሞ ነው። የጋብራ ብሔረሰብ አብዛኛው ኦሮሞ ሲሆን ቀሪው ሶማሌ ነው። የኦይዳ ብሔረሰብ ገሚሱ አሪ ገሚሱ ጋሞ/ጎፋ ነው።

ከላይ ከተዘረዘሩት ታሪካዊ ክስተቶች በመነሳት የብሔረሰብ ማንነት የሚለዋወጥ መሆኑን በግልጽ እንረዳለን። ወደፊት ኢትዮጵያ ውስጥ የትኞቹ ብሔረሰቦች እንደሚጣመሩ፣ እንደሚለያዩ፣ እንደሚከሰቱና እንደሚጠፉ መተንበይ ስለማይቻል ማንነትን ቋሚ አድርጎ መውሰድ ወደ ስህተት ያመራል። አንድ ቋንቋ የሚጋሩና ተመሳሳይ ባህል ያላቸውን የወላይታ፣ የጋሞ፣ የጎፋና የዳውሮ ሕዝቦች መጪው ትውልድ በሕዝቦች ስምምነትና መፈቃቀድ ወደ አንድ ማንነት ሊሰበስባችው ይችላል። ባይሶዎችና ሐሮዎች በስያሜ፣ በቋንቋና በአመጣጥ ልዩነት ስላለን ማንነታችን ለየብቻ ይረጋገጥልን ብለው ቢጠይቁ ሊገርመን አይችልም። የበርካታ ብሔረሰብ አባላት ተሰባጥረው በፍቅርና በሰላም በሚኖሩባቸው አካባቢዎች (ለምሳሌ ወልቃይት፣ ራያ፣ ድሬዳዋ፣ ሞያሌ እና ጭናቅሰን) ወደፊት አዳዲስ የብሔረሰብ ማንነቶች ቢከሰቱ እንደ ሌላ ተጨማሪ ክስተት እንጂ እንደ ተአምር አይታይም። ይህንን በድፍረት የምጽፈው ከታሪካዊ እውነታ በመነሳት ነው።

በታሪክ ወደኋላ ስንመለከት አንድ ያልተቀላቀለና ወጥነቱን ጠብቆ የመጣ ብሔረሰብ አናገኝም። በርካታ ብሔረሰቦች የተመሠረቱት ከበርካታ ብሔረሰቦች በተውጣጡ ጎሳዎች ነው። በዚህም የተነሳ አንዱ ብሔረሰብ ውስጥ የሚገኝ ጎሳ ሌላ ብሔረሰብ ውስጥም የሚገኝ ስለሆነ ብሔረሰቦቹ በጎሳ የተሳሰሩ ናቸው። ለምሳሌ ያህል ሐዲያ ውስጥ ከሚገኙት ጎሳዎች ውስጥ ሌሞ የሚባለው በኦሮሞ፣ በሲዳማና በአፋር ይገኛል። እንደዚሁም ቦያሞ የሚባለው ጎሳ በኦሮሞ፣ በጉራጌ እና በሶማሌ ይገኛል። ሶለቾ የሚባለው ጎሳ በኦሮሞ፣ በሶማሌና በአፋር የሚገኝ ሲሆን ባደጎ እና ሀይባ የሚባሉ ጎሳዎች በኦሮሞና በሶማሌ ይገኛሉ። ስለዚህ ሐዲያ ከኦሮሞ፣ ከሲዳማ፣ ከሶማሌ፣ ከአፋርና ከጉራጌ ጋር በዝምድና የተሳሰረ ነው።

ካምባታ ውስጥ ኤበጀና፣ ኤፈገና፣ መልጋ፣ ጁማ እና ፋርዛኖ የሚባሉ ጎሳዎች ሲዳማ ውስጥም የሚገኙ ሲሆን ገበራ፣ ገንዛ፣ መልጋ እና ገጃ የሚባሉት በኦሮሞም ይገኛሉ። ከአማራ የመጡ ናቸው የሚባሉ የካምባታ ጎሳዎች ጉልባ (ከቡልጋ)፣ ዶንጋ (ከጎጃም)፣ ጋፊትአማራ፣ እነጋርአማራ፣ ድልድለአማራ እና ዋቆአማራ ተብለው ይጠራሉ። ካምባታ ውስጥ ትግራ የሚባለውና ወላይታ ውስጥ ትግሬ የሚባለው ጎሳ አመጣጡ ከትግራይ ነው ይባላል። ከጎሳ አደረጃጀቱ የካምባታ ብሔረሰብ ከሲዳማ፣ ከኦሮሞ፣ ከአማራና ከትግራይ ብሔረሰቦች ጋር የሚዛመድ መሆኑን እናረጋግጣለን።

አማራና ትግራይ የጎሳ ሥርዓት ባይኖራቸውም ጎሳዊ ክፍፍል ወዳለበት ብሔረሰብ ሲደርሱ የጎሳ ማንነት ተሰጥቷቸው የተቀባይ ብሔረሰብ አካል ሆነው ይኖሩ እንደነበር፣ ቢያንስ ከካምባታና ከወላይታ የተገኘው የጎሳ አደረጃጀት ያመለክታል። ከላይ በዝርዝር ከተጠቀሱት አስረጂዎች ሁለት ቁምነገሮችን እንረዳለን። አንደኛው የብሔር ማንነት የግድ ተፈጥሮአዊና ዘላቂ አለመሆኑን ሲሆን፣ ሁለተኛው የብሔረሰቦች ጎሳዊ ትስስር ለማኅበረሰብ ሰላምና ለአገር አንድነት ሚና ያለው ዕሴት መሆኑ ነው።

የመሀል አገር ብሔረሰቦች ጎሳዊ ትስስር በከፊል

በደቡብ ኢትዮጵያ የሚገኙ ብሔረሰቦች በሙሉ ከላይ በተጠቀሰው አግባብ ከሌሎች ብሔረሰቦች ጋር በጎሳ የተሳሰሩ ናቸው። አንዳንድ ጊዜ ትስስሩ ድንበር አቋርጦ ወደ ጎረቤት አገሮች ይዘልቃል። ለምሳሌ ያህል የዳሰነች ብሔረሰብ የተመሠረተው በአገር ውስጥ ከሚገኙ ብሔረሰቦች ብቻ ሳይሆን ከሶማሊያ፣ ከኬንያና ከደቡብ ሱዳን አቅጣጫ በመጡ ሕዝቦችም ጭምር ነው። ከታች በምስሉ እንደተገለጸው ሺር ወይም እንካበሎ የሚባሉ ሕዝቦች ጋሪ ተብሎ ከሚጠራው የሶማሊያ ጎሳ፣ ኤሌሌ ከጋብራ ኦሮሞ፣ ራንዳል ከሬንዲሌ (ኬንያ)፣ ኮሮ ከሳምቡሩ (ኬንያ) እና ኦሮ ከዛሬዋ ደቡብ ሱዳን እንደመጡ ይነገራል።

ዳሳነቾች ማን ከየትና እንዴት እንደመጣ ከትውልድ ወደ ትውልድ በአፈ ታሪክ የጠለቀ ዕውቀት ያስተላልፋሉ። በመሆኑም የብሔረሰቡ አባላት ከየትኛው ሕዝብ ጋር እንደሚዛመዱ ጠንቅቀው ያውቃሉ። በዳሰነች ባህል መሠረት በተዛመዱ ሕዝቦች መሃል መጋደል ቀሳፊ ኃጢአት ተደርጎ ስለሚወሰድ ግጭት አስወግደው በሰላም ይኖራሉ። አንድ ስሪቱ ውህድ የሆነ ብሔረሰብ ከጎረቤት ብሔረሰቦች ጋር በልዩነት ውስጥ በሚገለጽ አንድነት የተቆራኘ ነው። ይህ እውነታ በቤተሰብ፣ በማኅበራዊ አንቂዎችና በትምህርት ካሪኩለም ተካቶ አዲሱ ትውልድ እንዲያውቀው ከተደረገ የዘመኑ የመከፋፈል ስሜት ተወግዶ የሕዝቦች የወንድማማችነትና የአንድነት ሥነ ልቦና እየተጠናከረ ይሄዳል።

የዳሳነች ብሔረሰብ አመጣጥ

የኢትዮጵያ ብሔር/ብሔረሰቦች ግንኙነት እጅግ የተሳሰረ በመሆኑ አንዱ ሌላውን ዘረኛና ጎሰኛ ብሎ ለመፈረጅ አመክንዮ የለውም። በተለምዶ ዘር ወይም ዘረኛ የሚለውን ቃል በተሳሳተ ትርጉም በመጠቀም ላይ እንገኛለን። ዘር በእንግሊዘኛ ሬስ (race) የሚለውን ቃል የሚወክል ሲሆን፣ የዓለም ሕዝብ በሦስት ዋና ዋና ዘሮች ይከፈላል። እነሱም ኮኮዞይድ (Caucasoid)፣ ሞንግሎይድ (Mongoloid) እና ነግሮይድ (Negroid) ናቸው። ጥቁር አፍሪካውያን በሙሉ የነግሮይድ ዘር ተደርገው ስለሚቆጠሩ አንዱ ከሌላው አንጻር ብሔርተኛ ወይም ጎሰኛ ቢሆን እንጂ ዘረኛ ሊባል አይችልም ምክንያቱም ሁሉም ጥቁር ሕዝቦች አንድ ዘር ናቸው።

ጎሳ (clan) በአንድ ብሔረሰብ ውስጥ የሚገኝ ስያሜ ያለው ንዑስ ቡድን ነው። ስለዚህ ጎሰኛ የሚለውን ቃል የምንጠቀመው በአንድ ብሔረሰብ አባላት መሀል የሚስተዋል ቡድናዊ ባህሪይን ለመግለጽ ነው። ነገር ግን በተለምዶ በተለያዩ ብሔረሰቦች አባላት መሀል ጎሰኝነት እንዳለ የሚገለጸው ስህተት ነው። የእነዚህ ቃላት አጠቃቀም የተሳሳተ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ለማሸማቀቅ የሚውሉ ስለሆነ ሕዝቦችን ከማቀራረብ ይልቅ ስለሚያራርቁ መታረም አለበት።

በደቡብ ኦሞ ዞንና በዙሪያው የሚገኙ ብሔረሰቦች ትስስር

ለማጠቃለል ያህል የብሔረሰቦች ድንበር ሲሰፋና ሲጠብ ማንነት ሊቀየር ይችላል። ማንነት ተቀየረ ሲባል ወደ ቀደመ ማንነት መመለስ ሊሆን ይችላል (ለምሳሌ እንደ ስልጤ፣ ሙርሌ፣ አሌ እና ቅማንት) ወይም እንደ አዲስ መፈጠር ይችላል (ለምሳሌ እንደ ጊድቾ እና ሌሎች በታሪክ ቀደም ብለው የተከሰቱት)። ነገር ግን የብሔረሰብ ማንነት መቀየርን ተከትሎ የሰዎች ዝምድና አይቋረጥም። ጉራጌና ስልጤ ቢለያዩም በሁለቱም ብሔረሰቦች የሚገኘው የዣራ ጎሳ፣ የእርስ በርስ ጋብቻና የረዥም ጊዜ አብሮነት ሥነ ልቦና ሁለቱን ሕዝቦች ያገናኛል። የቅማንት ብሔረሰባዊ ማንነት ተረጋገጠ ማለት በጋብቻ፣ በመዋለድና አብሮ በመኖር የተፈጠረው የአማራና የቅማንቴ የቆየ ዝምድና ያበቃለታል ማለት አይደለም። መሬት ላይ በተራው ሕዝብ መሀል ያለው የዕለት ተዕለት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት በአብዛኛው እንደነበረ ይቀጥላል።

አብዛኛዎቹ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በጎሳ፣ በጋብቻና በሌሎች ማኅበራዊ መስተጋብሮች የተቆራኙ ቢሆንም፣ ይህ ዕውቀት ትኩረት ተሰጥቶት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ባለመደረጉ በጉዳዩ የዘመኑ ወጣት ግንዛቤ እጅግ ዝቅተኛ ይመስላል። በዚህም የተነሳ የብሔር ማንነት ቋሚና ዘላቂ ይመስል በወንድማማችነት መተያየት የሚገባቸው ወገኖች ጎራ ለይተው በጠላትነት ተፈራርጀው ሲጋጩና ሲፋጩ ማየት ያማል። ስለዚህ በብሔረሰቦች መሀል ነባር ትስስር መኖሩን በሰብዕና ግንባታ አግባብ በቤተሰብና በትምህርት ተቋማት ደረጃ ማስገንዘብ ወዳጅነት እንዲጎለብት፣ ሰላም እንዲሰፍንና አገራዊ አንድነት እንዲጠናከር ይረዳል። በታዳጊ ወጣቶች ላይ ተፅዕኖ ማሳረፍ የሚችሉ ግለሰቦች፣ ማኅበራዊ አንቂዎችና ፖለቲከኞች ሕዝብ ከሚያራርቀው ይልቅ የሚያቀራርበውን መንገድ በማመልከት ገንቢ ሚና መጫወት ይኖርባቸዋል።

ጸሐፊው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአንትሮፖሎጂ ፕሮፌሰርና የጂንካ ዩኒቨርሲቲ መሥራች ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡ ከምርምር ሥራዎቻቸው መካከል የብሔረሰቦች ግንኙነት፣ የግጭት አፈታት ዘዴዎች፣ የአገር በቀል ዕውቀቶችና ልማዳዊ ሕጎች፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ሚና፣ እንዲሁም ሠፈራና የምግብ ዋስትናን የተመለከቱ ይገኙባቸዋል፡፡ አሁን የግል ተመራማሪና አማካሪ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል።

ምንጭ፦ ሪፖርተር ጋዜጣ August 20, 2023