ርዕሰ አንቀጽ

መሬት መሬት ሲያይ

አምስት ብር መንገድ ላይ ወድቆ ያገኘ አንድ ወጣት፣ ሌላም አገኝ እንደሆን ብሎ መሬት መሬቱን ሲያይ ረጅም ዓመታት አሳለፈ። በዓመታቱ መካከል ይኸው ወጣት ብዙ ነገር ለቃቀመ። ሃያ ዘጠኝ ሺህ አምስት መቶ አሥራ ስድስት አዝራሮችን፣ ሃምሳ አራት ሺህ አንድ መቶ ሰባ ሁለት የማስታወቂያ መርፌ ቁልፎችን እና አሥራ ሁለት ሳንቲም ለቀመ። ወፍራም መቀነት የማያስታግሰው የወገብ ህመምና ንፉግነትን አተረፈ። መሬት መሬት ሲያይ፣ አንድም ቀን ቀና ብሎ የማለዳ ፀሐይ ጮራዋን ስትፈነጥቅ ወይም የወዳጆቹን ፈገግታ ሆነ የአበቦችን ፍካታ ሳያይ ኖረ። መሬት መሬት እያዩ መጓዝ ኪሳራው የከፋ ነው። ምድር ላይ መኖር የራሱ ግዴታ ቢኖርበትም፣ ከምድር ጋር እንዲህ መቆራኘት፣ ማንነትን እና አቅጣጫን ማሳቱ አይቀርም።